ሳዑዲ አረቢያ ከአንድ ዓመት በፊት ጀምሬ ነበረ ያለችውን የፀረ-ሙስና ዘመቻ አጠናቅቄያለሁ ስትል አወጀች።
ከ14 ወራት በፊት ተጀምሮ በነበረው የፀረ-ሙስና ዘመቻ ትውልደ ኢትዮጵያዊው ቢሊየነር አሊ-አላሙዲንን ጨምሮ በመቶዎች ሚቆጠሩ የንጉሣዊያን ቤተሰብ አባላት እና ቢሊየነር ነጋዴዎች በቁጥጥር ሥር ውለው ነበር።
የሳዑዲ አረቢያ መንግሥት 100 ቢሊየን ዶላር በጥሬ ገንዘብ እና በቁስ መልክ በቁጥጥር ሥር ከዋሉት ሰዎች መሰብሰቡን አስታውቋል።
የባህር ሰላጤዋ ንጉሣዊ ግዛት አስተዳዳሪዎች እንደሚሉት ከሆነ በቁጥጥር ሥር ውለው ከነበሩት 87 ግለሰቦች የቀረበባቸውን ክስ በማመናቸው ከመግባባት ላይ ተደርሷል።
8ቱ ደግሞ የቀረበባቸውን ክስ ስላላመኑ ጉዳያቸው ለአቃቤ ሕግ ተላልፎ ተሰጥቷል።
56 ሰዎች ጉዳይ ደግሞ ውሳኔ ያላገኘ የወንጀል ክስ ስላለባቸው ጉዳያቸው አልተጠናቀቀም ተብሏል።
የሳዑዲ መንግሥት ያካሄደውን የፀረ-ሙስና ዘመቻን ተከትሎ በቁጥጥር ሥር ከዋሉት መካከል ሼህ መሐመድ ሁሴን አሊ-አላሙዲ ከቀናት በፊት ከእስር መለቀቃቸው ይታወሳል።
ሳዑዲ ወደ 200 የሚጠጉ ልዑላንን፣ ሚንስትሮችን እና የንግድ ኃላፊዎችን ሪያድ በሚገኘው ባለ 5 ኮከቡ ቅንጡ ‘ዘ ሪትዝ ካርልተን’ ሆቴል ውስጥ በቁጥጥር ሥር አቆይታ ነበር።
የፀረ-ሙስና ዘመቻው የተጀመረው ተጽዕኖ ፈጣሪነታቸው እየጨመረ በመጣው በልዑል አልጋ ወራሽ ሞሐመድ ቢን ሰልማን ነበር።
ልዑል አልጋ ወራሹ የሳዑዲ ጋዜጠኛ ጀማል ኻሾግጂ በኢስታንቡል የሳዑዲ ቆንስላ ውስጥ መገደሉን ተከትሎ ከፍተኛ ጫና ውስጥ ወድቀው ነበር።