ከእውቅ ሠዓሊያን አንዱ የሆነው ሊዩናርዶ ዳቪንቺ ሊሞት አካባቢ የነርቭ ህመም ገጥሞት እንደነበረ የጣልያን ሀኪሞች ተናግረዋል።
ሠዓሊው ህይወቱ ሊያልፍ አካባቢ የገጠመው የነርቭ ህመም ሥዕል እንዳይስል አግዶት ነበር ተብሏል።
ዳቪንቺ ሠዓሊ ብቻ ሳይሆን የሥነ ህንጻ ባለሙያና ቀራጺም ነበር።
ሀኪሞች እንዳሉት፤ ‘አንለር ፓልሲ’ የተባለው የነርቭ ችግር የእጁን እንቅስቃሴ ገድቦት ብሩሽ እንዳይዝ አግዶት ነበር። ህመሙ በስትሮክ ምክንያት እንደተከሰተበት መላ ምቶች አሉ።
በርካታ የሥነ ጥበብ ታሪክ አጥኚዎች ዳቪንቺ ይስል የነበረው በቀኙ ነው ወይስ በግራ እጁ በሚል ለዓመታት ተከራክረዋል።
ሀኪሞቹ ከድምዳሜ የደረሱት ሁለት የዳቪንቺ ሥዕሎችን ካጠኑ በኋላ ነበር። ሥዕሎቹ ከዚህ ዓለም በሞት ሊለይ አካባቢ የሠራቸው ሲሆኑ፤ አንደኛው የራሱ ግለ ምስል (ፖርትሬት) ነው።
በምስሉ ላይ ቀኝ ክንዱ ተሸፍኖ እጁም ተኮማትሮ ይታያል።
ሮም ውስጥ ያሉ የፕላስቲክ ቀዶ ጥገና ሀኪምና የምርምሩ መሪ ዶ/ር ዴቪዴ ላዘሪ እንደሚሉት፤ በምስሉ ላይ ያለው የዳቪንቺ እጅ ‘ክላው ሀንድ’ በሚል መጠሪያ የሚታወቀው የነርቭ በሽታን ያሳያል።
ዶ/ር ዴቪድ እንደሚሉት የዳቪንቺ የነርቭ ችግር ከስትሮክ ጋር የተገናኘ ላይሆን ይችላል። ምክንያቱም የአካሉ እንቅስቃሴ ሙሉ በሙሉ መገደቡን የሚያሳይ መረጃ የለም።
“በሠዓሊነት ሙያ በቆየባቸው የመጨረሻው አምስት ዓመታት፤ ሞና ሊዛን ጨምሮ በርካታ ሥዕሎችን ሳያጠናቅቅ የቀረው በህመሙ ምክንያት ሊሆን ይችላል” ብለዋል።
ሀኪሞቹ ለምርምር ከተጠቀሙባቸው ሥዕሎች በአንዱ የሙዚቃ መሣሪያ የሚጫወት ግለሰብ ይታያል። ግለሰቡ ዳቪንቺ እንደሆነ በቅርቡ ተደርሶበታል።
አንቶኒዮ ደ ቢያቲስ እንደጻፈው፤ ዳቪንቺ በስተመጨረሻ ዘመኑ ቀኝ እጁ አልታዘዝ ብሎት ስለነበረ ጥሩ ሥዕል መሥራት አልቻለም ነበር።
ምንጭ፡ ቢቢሲ