ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን በተመለከተ በኢትዮጵያ፣ በግብፅና በሱዳን መካከል ሲደረግ በነበረው ድርድር መግባባት ያልተደረሰባቸው ጉዳዮች ለመሪዎች ውሳኔ እንዲቀርብ የአፍሪካ ኅብረት አሳሰበ፡፡
የሦስቱ አገሮች ተደራዳሪዎች በዚህኛው ዙር ድርድራቸው አዲስ የድርድር አካሄድን መከተል ይገባል በሚል በሱዳንና በኢትዮጵያ ተቀባይነት ያገኘ ሐሳብ ተራምዶ የነበረ ቢሆንም፣ ይህንን ሐሳብ ግን ግብፅ ሳትቀበለው ቀርታለች፡፡ በሱዳንና በኢትዮጵያ በኩል የቀረበው አዲስ የድርድር አማራጭ፣ በአሁኑ ወቅት እያደራደረ የሚገኘው የአፍሪካ ኅብረት ሚና ማሳደግ የሚል ነው፡፡
በዚሁ አማራጭ መሠረትም ከተለያዩ የአፍሪካ አገሮች ሁለት ሁለት ባለሙያዎች በድርድሩ እንዲሳተፉ ማድረግና የአፍሪካዊያንን ችግር በአፍሪካውያን የመቅረፍ መርህ ድርድሩ እንዲካሄድ የሚል ነበር፡፡
ይህንን አማራጭ ኢትዮጵያና ሱዳና ደግፈው ያቀረቡ ቢሆንም፣ በግብፅ በኩል ግን ተቃውሞ ገጥሞታል፡፡
በዚህ ጉዳይ ላይ ዕልባት ለመስጠት ሐሙስ ኅዳር 10 ቀን 2013 ዓ.ም.፣ ድርድሩ በሦስቱ አገሮች የውኃ ጉዳይ ሚኒስትሮች አማካይነት በቪዲዮ ኮንፈረንስ ተካሄዶ የነበረ ቢሆንም ውጤት አልተገኘበትም፡፡
‹‹የድርድሩ አካሄድ ካልተለወጠ በድርድሩ አልሳተፍም›› የሚል አቋም የሱዳን መንግሥት ተደራዳሪዎች ማራመዳቸውን፣ የኢትዮጵያ የውኃ መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስቴር ያወጣው መግለጫ ያመለክታል፡፡
በዚህ ጉዳይ ላይ መፍትሔ ባለመገኘቱም የአደራዳሪነት ሚና የያዘው የአፍሪካ ኅብረት አስፈጻሚ ምክር ቤት ሦስቱ አገሮች ውይይት አድርገው፣ በሚቀጥለው ሳምንት ለሦስቱ አገሮች መሪዎች የሚቀርብ የተጨበጠ ነገር ላይ እንዲደርሱ በማሳሰብ ስብሰባው በዚያው ቀን መጠናቀቁን ለመረዳት ተችሏል፡፡