የሚንስትሮች ምክር ቤት በትላንትናው እለት በትግራይ ክልል ላይ ተግባራዊ እንዲደረግ ያወጀውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የህዝብ ተወካዮች ምር ቤት አጸደቀ፡፡
የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጥቅምት 26 ቀን 2013 ዓም ባካሄደው ስብሰባ፣ በትግራይ ክልል ላይ ለስድስት ወራት እንዲጣል የተወሰነውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አጽድቋል፡፡
አስቸኳይ አዋጁን የሚያስፈጽም ግብረኃይል የሚቋቋም ሲሆን ተጠሪነቱም ለጠቅላይ ሚንስትሩ እንደሚሆን በአዋጁ ተደንግጓል፡፡
ግብረኃይሉ በጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ጄነራል አደም መሐመድ የሚመራ መሆኑም ታውቋል፡፡
የሚኒስትሮች ምክር ቤት ጥቅምት 25 ቀን 2013 ዓ.ም ባደረገው ልዩ ስብሰባ፥ በትግራይ ብሔራዊ ክልል ውስጥ ሕገ መንግሥቱንና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን እንዲሁም የሕዝብን ሰላምና ፀጥታ አደጋ ላይ የሚጥሉ በተለይም የሀገርን ሉዐላዊነት የሚገዳደሩ ጉዳዮችን በሚመለከት፣ የፌደራል መንግሥት በሕገ መንግሥቱ የተሰጠውን ሥልጣንና ኃላፊነት በክልሉ እንዲወጣ እና ሀገሪቷን የጦር አውድማ የሚያደርጉ፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ውሳኔዎችን ጭምር በመጣስ በርካታ ሕገ ወጥ ተግባራት እየተፈፀሙ በመሆኑ፤ ይህን ሁኔታ በመደበኛው የሕግ ማስከበር ሥርዓት ለመከላከልና ለመቆጣጠር የማይቻልበት ደረጃ ላይ መደረሱን በመረዳት፤ በሕገ መንግሥቱ በተደነገገው መሠረት ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን ለመጠበቅ ልዩ እርምጃዎችን መውሰድ የሚያስችል የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 93/1/ሀ ድንጋጌ መሰረት አውጇል፡፡
ምንጭ፡ ሪፖርተር