በኒውዮርክ እስረኛ ቤተሰቦቻቸውን፣ ዘመዶቻቸውንና ወዳጆቻቸውን ሊጠይቁ የመጡ ግለሰቦች ኤሌክትሪክ መቋረጡን ተከትሎ በእስር ቤቱ በመታገታቸው ምክንያት ተቃውሞ አስነስተዋል።
በብሩክሊን የሚገኘው የፌደራል እስር ቤት አካል የሆነው ሜትሮፖሊታን የተሰኘው እስር ቤት ውጭ ላይ ” ሙቀት የለም፣ መብራቱ?” የሚሉ መፈክሮችን በመያዝ ድምፃቸውን ያሰሙ እንደነበር ተዘግቧል።
ብዙ እስረኞች ከውጭው አለም ጋር ያላቸው ግንኙነት ተቋርጧል ተብሏል።
ቅዳሜ እለት እስር ቤቱን የጎበኙ የምክር ቤት አባላት ጉዳዩን ” ሰቆቃ የተሞላበት” ብለውታል።
ከድጡ ወደ ማጡ እንዲሉ የክረምቱ ቀዝቃዛ ችግሩን የበለጠ ያከበደው ሲሆን ፤ በእስር ቤቱ 9.5 ዲግሪ ሴንቲግሬድ ዝቅተኛ የሆነ ሙቀት መጠን ተመዝግቧል።
ጄሮልድ ናድለር የተባለ የኒውዮርክ ምክር ቤት አባል የእስር ቤቱን ባለስልጣናት አፋጣኝ እርምጃ ባለመውሰድና በቸልተኝነት ወንጅለዋቸዋል።
ከ1600 በላይ እስረኞች ባሉበት እስር ቤት ውጭ ለተሰበሰቡ ግለሰቦች ጄሮልድ እንደተናገሩት ችግሩን ለመቅረፍ እየሰሩ እንደሆነና ሰኞ ዕለት መብራት ሊመለስ እንደሚችል ነው።
ተቃዋሚዎቹ ” እስር ቤቱ ይዘጋ”፤ “እንግልት በእስር ቤቱ ውስጥ”፤ “ሙቀቱን ከፍ አድርጉት” የሚሉ መፈክሮችን ይዘው ነበር።
አንደኛው ግለሰብ በትዊተር ገፁ እንዳሰፈረው ሰልፈኞቹ መፈክራቸውን በሚያሰሙበት ወቅት እስረኞቹ መስኮቶቹን በመደብደብ ላይ ነበሩ ብሏል።
የአካባቢው ባለስልጣናት እንዳስረዱት የችግሩ መነሻ እሳት ተነስቶ የአካባቢውን የኤሌክትሪክ መስመር በማበላሸቱ ነው።
የእሳት አደጋው በተጨማሪ መጠባበቂያ ጄኔረተር ማብሪያና ማጥፊያውንም አቃጥሎታል።
የፌደራል የእስረኞች አስተዳደር በበኩሉ መብራቱን ለመመለስ ጠንክረው እየሰሩ እንደሆነና ለጊዜው እስረኞች የግል ንፅህናቸውን የሚጠብቁበት ሙቅ ውሃ እንዳለና የህክምና አገልግሎትም እንዳልተቋረጠ ተናግረዋል።
አስተዳደሩ ጨምሮም ህንፃው ለድንገተኛ ጊዜ የሚሆን መብራት እንዳለው ነው።
ቅዳሜ አመሻሹ ላይ የከተማዋ ከንቲባ ቢል ዴ ብላሲዮ በበኩላቸው የፌደራል ባለስልጣናትን አውግዘው የከተማዋ ባለስልጣናትም ችግሩን ለመቆጣጠር ለእስረኞች ብርድ ልብስ እየሰጡ ነው ብለዋል።