የኦሮሞ ነጻነት ግንባር /ኦነግ/ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ከፈቀደለት በዘንድሮው ጠቅላላ ምርጫ እንደሚወዳደር አስታወቀ። ፓርቲው ለሁለት ቀናት ያካሄደውን ጠቅላላ ጉባኤ አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል።
በመግለጫው ህጋዊና ሠላማዊ ትግሉን አጠናክሮ የሚቀጥል መሆን ገልጿል።
ኦነግ በመግለጫው ህጋዊና ሠላማዊ የፖለቲካ ትግሉን አጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን ገልፆ በተለያዩ ቦታዎች እየታዩ ያሉ ግድያዎች እንዲወገዱና ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍን እንደሚሰራ አረጋግጧል።
“የኦሮሞን ህዝብ ፍላጎት የሚያሣካው ሰላማዊ ትግል ብቻ ነው” ያለው ፓርቲው በመግለጫው ሁሉም ህዝብ ለሰላም ዋጋ መስጠት አለበት ብሏል።
ሰርዓት አልበኝነትና ህገ-ወጥነት እንዲወገድም ህዝቡ የበኩሉን እንዲያደርግ ጥሪ አቅርቧል፡፡
የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) 2ኛ ጠቅላላ ጉባኤውን የመርጫ ቦርድ ተወካዮች በተገኙበት ማድረጉን የገለጸ ሲሆን በዚህም የአመራር ለውጥ ማድረጉን ይፋ አድርጓል።
በዚህ ዓመት ለሚካሄደው 6ኛ ጠቅላላ ምርጫም ከኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ፈቃድ የሚያገኝ ከሆነ የሚወዳደር መሆኑን አስታውቋል፡፡
ምርጫ ቦርድም ኦነግ የነበረበትንና ያለበትን ወቅታዊ ሁኔታ ከግምት በማስገባት ለምርጫ የሚቀርቡ ተወዳዳሪዎችን እንዲመዘግብለት ጠይቋል።
ፓርቲው በመግለጫው ለሀገሪቱ ሰላም፣ ህብረ ብሄራዊ ፌደራሊዝም እንዲሁም ለዴሞክራሲ እኩልነት ከሚሰሩ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር በጋራ ለመስራት ዝግጁ መሆኑን አረጋግጧል።
ፓርቲው ለሌሎች የፖለቲካ ፓርቲዎች ዓላማና ሃሳብም ከበሬታ ያለው መሆኑን ገልጾል፡፡
በአሁኑ ጊዜ አገሪቷን እየመራ የሚገኘው መንግስት የህዝቦችን ደህንነትና ሰብዓዊ መብት ለማስከበር የጀመረውን ስራ አጠናክሮ እንዲቀጥልም ፓርቲው በመግለጫው አስታውሷል፡፡
የደህንነት ስጋትና የፖለቲካ አለመግባባት ተወግዶ አገሪቷ ወደ እውነተኛ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ለማሻገር እንዲቻልም መንግስት ሃላፊነቱን እንዲወጣም ጠይቋል፡፡
ኦነግ ባካሄደው 2ኛ ጠቅላላ ጉባኤ አቶ አራርሶ ቢቂላ የግንባሩ ሊቀመንበር አድርጎ የመረጠ ሲሆን አቶ ቀጄላ መርዳሳንና አቶ ብርሃኑ ለማን ምክትል ሊቀመንበር አድርጎ መምረጡን አስታውቋል።
በተጨማሪም በጠቅላላ ጉባኤው 43 ቋሚና 5 ተለዋጭ የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት መመረጣቸውን ከፓርቲው ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡
ለዘንድሮው ጠቅላላ ምርጫ በጊዜ ሰሌዳው መሰረት የተመራጮች ምዝገባ ቀን መጠናቀቁ ይታወቃል።