ጦላይ ወታደራዊ ማሠልጠኛ የገባው የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) ያጋጠመው ጦር የምግብ መመረዝ ተጣርቶ ለሕዝብ ይፋ እንዲደረግ ኦነግ ጠየቀ፡፡
የኦነግ ጦር አባላት እሑድ ሚያዝያ 6 ቀን 2011 ዓ.ም. ማለዳ ቁርስ ላይ ሻይ ሲጠጡ በመመረዛቸው ምክንያት የሆድ ቁርጠትና ትውከት እንዳጋጠማቸው ታውቋል፡፡ በወሊሶ ከተማም ሕክምና የተደረገላቸው ሲሆን፣ ከሕመም በስተቀር ሌላ የከፋ ጉዳት አለመድረሱ ተገልጿል፡፡
ግንባሩ በመግለጫው የኦሮሞ ነፃነት ጦር አባላት አባ ገዳዎች ባደረጉላቸው ጥሪ መሠረት ትጥቃቸውን ለአባ ገዳዎች አስረክበው ጦላይ ወታደራዊ ማሠልጠኛ ከገቡ በኋላ፣ እሑድ ሚያዚያ 6 ቀን 2011 ዓ.ም. የበሉት ቁርስ የተበከለ በመሆኑ ምክንያት ከ200 በላይ የሆኑት ለአጣዳፊ በሽታ መጋለጣቸውን አስታውቋል፡፡ ‹‹ይኼ ዜና በጣም ያስደነገጠን፣ ያሳዘነንና የረበሸን መሆኑን መግለጽ እንወዳለን፤›› ሲል ኦነግ በመግለጫው አስታውቋል፡፡
“በአባ ገዳዎች የተቋቋመው ቡድን በኦሮሞ ነፃነት ጉዳይ ላይ ተጠያቂነትን የወሰደ በመሆኑ፣ ጉዳዩን ተከታትሎ በፍጥነት እንዲያጣራ አጥብቀን እንጠይቃለን፡፡ መንግሥትም በእጁ ያሉትን ሌሎች የኦሮሞ ነፃነት ጦር አባላት ተገቢውን እንክብካቤ በማድረግ ተጠያቂነቱን እንዲወጣ ደግመን እናሳስባለን፤›› ሲል ግንባሩ አክሏል።
‹‹ሕዝባችንም ይኼን ጉዳይ በንቃት ተከታትሎ የታጋዮቹ ጉዳይ ትኩረት እንዲያገኝ አስፈላጊውን ጫና በመፍጠር፣ ለኦነግ የተሰጠውን ኃላፊነት እንዲደግፍ እንጠይቃለን፤›› ብሏል፡፡
በጦላይ ማሠልጠኛ ያሉት የኦነግ ጦር አባላት የምግብ መመረዝ እንደገጠማቸው ከተሰማ በኋላ በተለይ የወሊሶ ከተማና የአካባቢው ነዋሪዎች፣ ሰኞ ሚያዝያ 7 ቀን 2011 ዓ.ም. ከማለዳ ጀምሮ የተቃውሞ አድማ አድርገዋል፡፡
በአድማው ምክንያት ከወሊሶ ወደ አዲስ አበባ፣ እንዲሁም ከአዲስ አበባ ወደ ወሊሶ የሕዝብ ማመላለሻ የትራንስፖርት አገልግሎቶች እንዳይገቡና እንዳይወጡ ወጣቶች መንገድ በመዝጋት፣ በከተማዋ ሌሎች ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ አገልግሎቶችም በአድማው ምክንያት እንዲቋረጡ አድርገዋል፡፡ የመንግሥት ተቋማትና ትምህርት ቤቶችም ዝግ ነበሩ።
ከመንግሥት ጋር በተደረገ ስምምነት መሠረት ትጥቅ ፈትተው ወደ ጦላይ ካምፕ እንዲገቡ ከተደረጉ የኦነግ ጦር አባላት ውስጥ ሁለት መቶ የሚሆኑት በምግብ ተመርዘዋል መባሉ፣ በከተማዋ ለተቀሰቀሰው የተቃውሞ አድማ ምክንያት መሆኑን ሪፖርተር ያነጋገራቸው የከተማዋ ወጣቶች ገልጸዋል።
ለተቃውሞ የወጡ ወጣቶች የኦሮሚያ ክልልን በሚመራው የኦሮሞ ዴሞክራቲክ ፓርቲ (ኦዴፓ) ላይ ያነጣጠሩ ወቀሳዎችን ሲሰነዝሩ ተሰምተዋል።
ጉዳዩን በተመለከተ የኦሮሚያ ክልል የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አድማሱ ዳምጠው እንደገለጹት፣ እሑድ ሚያዚያ 6 ቀን 2011 ዓ.ም. ከማለዳው አንድ ሰዓት አካባቢ በጦላይ ሥልጠና ማዕከል ውስጥ ያሉ የተወሰኑ የኦነግ ሠራዊት አባላት የጤና እክል ገጥሟቸው ሆስፒታል ገብተዋል፡፡ በሥልጠና ማዕከሉ የተከሰተው ችግር መንስዔም በመጣራት ላይ ነው ብለዋል። የክልሉ ፖሊስም በምርመራ ላይ መሆኑን አስታውቋል፡፡