ከአዲስ አበባ ወደ ሌጎስ 393 መንገደኞችን ያሳፈረው የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን በረራ ቁጥር ኢቲ 901 ፣ ቦይንግ 777 በረራ በኢትዮጵያዊው ፓይለት ችሎታ የ 393 ሰዎች ህይወት ተረፈ
በዚህ በረራ ውስጥ የቀድሞ የናይጄሪያ ፕሬዚዳንት ኦባሳንጆን ጨምሮ በርካታ የናይጄሪያ ባለሥልጣናትም ነበሩበት። አምስት ሰዓት የሚፈጀው በረራ በሰላምና ደስ በሚል ሁኔታ ተጠናቆ፣ ሌጎስ አየር ማረፊያ ደረሰ፣ ነገር ግን በወቅቱ ዝናብና ነፋስ ስለነበረ አውሮፕላኑ መሬት መንካት የነበረበትን የመጀመሪያ ረድፍ አልፎ ሶስተኛው መስመር ላይ መሬት ይነካል (ተች ዳውን) ። ነገር ግን ፓይለቱ መሬት የነካበት ቦታ ትክክል እንዳልሆነ ወዲያው በመረዳቱ መልሶ አውሮፕላኑን በማንሳት እንደ ገና አየር ላይ ይወጣል።
ነገሩ ወዲያው ያልገባቸው ተሳፋሪዎችና የአውሮፕላኑ ሰራተኞች በሙሉ በድንጋጢ ክው ይላሉ። በውስጡ የነበሩ ሰዎች ለዜና አውታሮች ሲናገሩ “ሁሉም ሰው መጸለይ ጀመረ፣ በቅርብ የነበረው አደጋው በህሊናቸው የመጣ ይመስላል፣ እየጮሁ የሚጸልዩ ሁሉ ነበሩ” ነበር ያለው።አውሮፕላኑም 20 ደቂቃ ያህል በሌጎስ ሰማይ ላይ ከዞረ በኋላ ተመልሶ በትክክለኛው ቦታ መሬት በመንካት አውሮፕላኑን በሰላም ሊያሳርፍ ችሏል።
የናይጄሪያ አየር መንገድ የመንገደኞች ጉዳይ ሃላፊ የሆኑት ኦቶሪ ጂሞህ በበኩላቸው ሲናገሩ “አውሮፕላኑ መጀመሪያ መሬት እንደነካ በዚያው ቀጥሎ ቢሆን ኖሮ፣ የመጨረሻው ማቆሚያ ለመድረስ መንገዱ ሰለሚያጥር በዚያው ፍጥነቱ ተጉዞ ትልቅ አደጋ ሊፈጠር፣ የመንገደኞች ህይወትም አደጋ ላይ ሊወድቅ ይችል ነበር፣ ነገር ግን ፓይለቱ ልምድ ስላለው መልሶ በማንሳት እንደገና በሚገባ አርፏል” ማለታቸውን sahara reporters ተሳፋሪዎችን ጠቅሶ ዛሬ ዘግቧል::