(ኤ.ቢ.ሲ) የአልኮል መጠጥ በብሮድካስት አማካኝነት ማስተዋወቅ የሚከለክለው ድንጋጌ ከዛሬ ጀምሮ ተፈጻሚ ይሆናል።
የምግብ እና የመድኃኒት አስተዳደር አዋጅ ቁጥር 1112 በፌደራል ነጋሪት ጋዜጣ የካቲት 21 ቀን 2011 ዓ.ም ታትሞ መውጣቱ ይታወሳል።
በአዋጁ አንቀጽ 74 (4) መሰረት የአልኮል መጠጥ በብሮድካስት (ቴሌቪዥን እና ሬድዮ) አማካኝነት ማስተዋወቅ የሚከለክለው ድንጋጌ ከዛሬ ግንቦት 21 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ ተፈጻሚ እንደሚሆን ነው የጤና ሚኒስትሩ ዶክተር አሚር አማን ያስታወቁት።
በዚሁ መሰረት ከዛሬ ጅምሮ ማንኛውም የብሮድካስት ሚድያ የአልኮል መጠጥ የማስታወቂያ ማስተላለፈፍ እንደማይችሉ ነው ሚኒስሩ አስታውቀዋል፡፡
እንዲሁም በተለያዩ አከባቢዎች የሚገኙ ቢልቦርዶች መነሳት እንዳለባቸው ነው የተነገረው፡፡
የምግብ እና የመድኃኒት አስተዳደር አዋጅ ቁጥር 1112 ባሳለፍነው ጥር 28 ቀን 2011 ዓ.ም በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መፅደቁ ይታወሳል።
አዋጁ የአልኮል መጠጥ በብሮድካስት (ቴሌቪዥን እና ሬድዮ) አማካኝነት ማስተዋወቅን ሙሉ በሙሉ ክልክል መሆኑን ደንግጓል።
እንዲሁም በአዋጁ እድሜያቸው ከ21 ዓመት በታች ለሆኑ ሰዎች የአልኮል መጠጥ መሸጥን የሚከለክል ሲሆን፥ በኢትዮጵያ የደረጃዎች ኤጄንሲ በጸደቀው ደረጃ መሰረት ትክክለኛው የአልኮል ትርጉም 0.5 እንዲሆን ደንግጓል።