ከኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ጊምቢ ዞን ቶሌ ቀበሌ ለደኅንነታቸው የሰጉ 64 ተፈናቃዮች ወደ አዲስ አበባ ሲመጡ ሆለታ ላይ በአካባቢው በሚገኙ በመንግሥት የፀጥታ አካላት ወደነበሩበት ለመመለስ መገደዳቸውን ለአዲስ ማለዳ አስታወቁ።
ቅሬታቸውን ለአዲስ ማለዳ የተናገሩ ዜጎች፣ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ጊምቢ ዞን ቶሌ ቀበሌ አሁንም ቢሆን የፀጥታው ሁኔታ አስተማማኝ ነው ማለት እንደማይቻል እና ብዙ ሰዎች ከመኖሪያ ቤታቸው ተፈናቅለው መጠለያ ጣቢያ እንዲሁም ወደተለያዩ ቦታዎች እየተሰደዱ ይገኛሉ ብለዋል።
አክለውም፣ ለደኅንነታቸው የሰጉ 64 የሚሆኑ ሰዎች ከሚኖሩበት አካባቢ ሰኔ 29 ቀን 2014፣ 7 መቶ ብር የትራንስፖርት ክፍያ በመፈፀም ወደ አዲስ አበባ ከተማ እየመጡ ሳለ ሆለታ ከተማ ሲደርሱ፣ በአካባቢው ባለ የፖሊስ እና በፀጥታ አስከባሪ አካላት ወደ መጡበት አካባቢ ለመመለስ እንደተገደዱ ገልጸዋል።