አዲስ አባባ፣ግንቦት 5፣ 2011 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት አቃቤ ህግ በአቶ በረከት ስምዖን እና አቶ ታደሰ ካሳ ላይ አሉኝ ያላቸውን የቃል ምስክሮች ከግንቦት 21 ጀምሮ እንዲያሰማ ቀጠሮ ሰጠ።
ፍርድ ቤቱ ባለፈው ዓርብ አቶ በረከት ስምዖን ያቀቡትን የእምነት ክህደት ቃል መቀበሉ ይታወሳል።
በዛሬው ውሎውም የአቶ ታደሰ ካሳን የእምነት ክህደት ቃል የተቀበለ ሲሆን ፥ተከሰሹ በተከሰሰባቸው ጉዳዮች ላይ ምንም አይነት ጥፋት አለመፈጸማቸውን በመጥቀስ ወንጀለኛ አለመሆናቸውን ገልፀዋል።
ከሳሽ አቃቤ ህግ በበኩሉ ተከሳሹ አልፈፀምኳቸውም ባሉት ጉዳይ ላይ በርካታ የሰው ምስክሮች እንዳሉት ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል።
ሁለቱ ተከሳሾች ጠበቃ የማቆም አቅሙና ፍላጎቱ እያላቸው እስካሁን ግን ማቆም እንዳልቻሉ ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል።
ጠበቃ ማቆም ያልቻሉተም በሚያቆሟቸው ጠበቃዎች ላይ ልዩ ጥበቃ ባለመደረጉ ምክንያት ማስፈራሪያና ዛቻ
ስለሚደርስባቸው ነው ብለዋል።
የግራ ቀኙን ክርክር ያዳመጠው ፍርድ ቤቱም ዓቃቤ ህግ አሉኝ ያላቸውን የቃል ምስክሮች ከግንቦት 21 ቀን 2011 ዓ.ም ጀምሮ እንዲያሰማ ቀጠሮ ሰጥቷል።
በተጨማሪም ፍርድ ቤቱ ተከሳሾች ከቀጠሮው በፊት ጠበቃ ፈልገው በፅሁፍ እንዲያቀርቡ ትዕዘዝ የሰጠ ሲሆን፥ለሚያቆሟቸው ጠበቃዎችም ልዩ ጥበቃ እንደሚደረግላቸው አሳውቋል።
በጥረት ኮርፖሬት የሀብት ምዝበራ ተጠርጥረው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታየ የሚገኙት አቶ በረከት ስምዖን እና አቶ ታደሰ ካሳ በሙስና እና ስራን ባመች ሁኔታ ባለመስራት ወንጀሎች አራት ክሶች የተመሰረቱባቸው መሆኑ ይታወሳል።
ምንጭ: Fanabc