የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ኮርነር ስቶን ሀውሲንግ ደቨሎፕመንት ግሩፕ ከተሰኘ ድርጅት ጋር በሀዋሳ ኢንዱስተሪያል ፓርክ ለፋብሪካ ሰራተኞች የመኖሪያ ቤት ግንባታ ለመፈፀም የሚያስችል የውል ስምምነት ተፈራርሟል፡፡
ኮርፖሬሽኑ በፋብሪካ ውስጥ የሚሰሩ ሰራተኞች ያለባቸውን የመኖሪያ ቤት ችግርን ለመቅረፍ የሚያስችል የመኖሪያ ቤቶች ግንባትን በሀዋሳ ኢንዱስትሪያል ፓርክ ለማካሄድ ዛሬ የውል ስምምነት የፈፀመው፡፡
የመኖሪያ ቤት ግንባታውን ለማከሄድ የሚያስችለውን የውል ስምምነት የኮርፖሬሽኑ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ሳንዶካን ደበበ እና የኮርነር ስቶን ሀውሲንግ ደቨሎፕመንት ግሩፕ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ሲራክ አምባዬ ተፈራርመውታል፡፡
ለሀዋሳ ኢንዱስትሪያል ፓርክ ለ6500 የፋብሪካ ሰራተኞች የመኖሪያ ቤት ለማቅረብ ኮርነር ስቶን ሀውሲንግ ደቨሎፕመንት ግሩፕ ከተባለ ኩባንያ ጋር ዛሬ የውል ሥምምነት የተካሄደ ሲሆን ፕሮጀክቱም በ 2.08 ሄክታር ላይ የሚያርፍ ይሆናል ተብሏል፡፡
የመኖሪያ ቤት ግንባታው ተጠናቆ አገልግሎት ላይ ሲውል ከሰራተኞች መኖሪያነት ባሻገር የሰራተኞች መመገቢያ አዳራሾች፣ ሱቆች፣መዝናኛ ቦታዎች፣ባንክ፣ የሰራተኞች ስልጠና መስጫዎች፣ አረንጓዴ ስፍራ፣ክሊኒክ እና ቢሮዎችን ያካተተ እንደሚሆን ተነግሯል፡፤በሀዋሳ ኢንዱስትሪያል ፓርክ የሚገነባው ይህ ፕሮጀክት 13 ሕንጻዎችን ያካተተ ሲሆን የግንባታ ሂደቱም በ18 ወራት ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡